አቤ ቶኪቻው
ወሬውን ያገኘሁት ከወዳጃችን አርአያ ነው፤ እስቲ ውረደው አርአያ…
የኢህአዴግ ቀይ እስክሪብቶ የተሰኘው የጋዜጠኛና መምህርት ርዕዮት አለሙ መጽሐፍ ቅዳሜ ሐምሌ 28 2004ዓ.ም ከቀኑ በ9 ሰዓት በራስ አምባ ሆቴል ይመረቃል፡፡ በምረቃ ስነስርዓቱ ላይ ፕ/ር መስፍን ወ/ማርያም፣ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ እና ጋዜጠኛ ሰርካለም ፋሲል በክብር እንግድነት የሚገኙ ሲሆን በርካታ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች ተመስገን ደሳለኝን ጨምሮ ታዋቂ ሰዎች እንዲታደሙ ተጋብዘዋል፡፡
መጽሐፉ በአሁኑ ሰዓት የ14 አመት ፍርደኛ ሆና በቃሊቲ ማረሚያ ቤት የምትገኘው ጋዜጠኛና መምህርት ርዕዮት አለሙ በተለያዩ ጊዜያት በአዲስ ፕሬስ፣ በአውራምባ ታይምስ፣ በፍትህ ጋዜጦችና በቼንጅ መጽሔት ላይ ካቀረበቻቸው ፖለቲካዊ ትንታኔዎች ውስጥ የተመረጡ 20 ጽሑፎችን ያካተተ ነው፡፡ እነዚህ የተመረጡ 20 ጽሑፎች ትኩረት ያደረጉት በሀገራችን ወቅታዊ የፖለቲካ ጉዳይ ላይ ሲሆን በተለይም ኢህአዴግ ከምርጫ 97 ወዲህ ጀምሮ “አውራ ፓርቲ ነኝ” እስካለበት ጊዜ ድረስ የሄደበትን አስከፊ የፖለቲካ ጉዞ የሚተነትኑና ሂደቱ እያስከተለ ያለውን ሀገራዊ መዘዝ በስፋት ይዳስሳሉ፡፡
204 ገጾች ያሉት ይህ መጽሐፍ ለአንባብያን ምቹ በሆነ ሁኔታ በአራት ክፍል የተደራጀ ሲሆን በምረቃው ማግስት በ40 ብር ለገበያ ይቀርባል፡፡
ወዳጅ አርአያን አመስግኜ፣ ይህ በእንዲህ እንዳለ… ብዬ እኔ ስቀጥል፤
ጋዜጠኛይቱ እና መምህርቷ ርዕዮት “አሸብረሻል” በሚል የተፈረደባትን የአስራ አራት አመት እስራት እና ሰላሳ ምናምን ሺህ ብር ቅጣት ተቃውማ ይግባኝ መጠየቋ ይታወቃል። ይኸው ይግባኝ በዛሬው እለት ውሳኔ ያገኛል ተብሎ ይጠበቃል። ወደ ኋላ ላይ ወሬ ካገኘሁ ለማቀብል የማልሰንፍ መሆኔን እገልፃለሁ።
© 2012, ↑ Ethiopian News in Amharic
Log in- Posts - Add New - Powered by WordPress - Designed by Gabfire Themes
2 Responses to “የኢህአዴግ ቀይ እስክርቢቶ” የተሰኘው የርዕዮት አለሙ መፅሐፍ ሊመረቅ ነው!